የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሞት ለእኛ ድኅነት እንደሆነ ቅዱስ መጽሐፉ ያስረዳል። ስለዚህ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በሰፊው አብራርቶልናል። “የሰው ልጅ በራሱ ጥፋት በሞት ጥላ ሥር ቢወድቅም መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በሞቱ ደምስሶ ለሚያምኑበት ሕይወትን ድኅነትን አውጇል። “አሁን ግን ክርስቶስ ለአንቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተለይቶ ከሞት ተነስቶአል።” (፩ኛ ቆሮ.፲፭፥፳-፳፩) ሐዋርያውና ወንጌላዊው ማቴዎስ እንደጻፈው ኢየሱስ እኛን ከድካማችን ሁሉ ለማሳረፍ በእርሱም ዘንድ እረፍትን እንድናገኝ በቃሉ እንደጋበዘን ሲያስረዳን “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ” (ማቴ. ፲፩፥፳፰) እያለ ጥሪውን ያስተላልፋል። ስለዚህ ቤተክርስቲያናችንም ይህንን ቅዱስ ቃል መርሆ በማድረግ ወደ እግዚአብሔር ቤት ምዕመናንን በየጊዜው ትጋብዛለች። አሁንም እንኳን ለብርሃነ ትንሣዔው በሰላምና በሕይወት አደረሳችሁ እያልን እርስዎ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣዔና ሕይወት ተካፋይ እንዲሆኑ በቅድስት ቤተክርስቲያናችን ስም ጥሪ እናቀርባለን። ይህም ጥሪ የእግዚአብሔር እንጂ ከሰው እንዳይደለ ክፍ ብሎ ተገልጿል። የእግዚአብሔርንም ጥሪ የተቀበሉ በእርሱ የሚመሩ በደስታ ይኖራሉ። የፈለጉት ሁሉ ይፈጸምላቸዋል። ይህንንም ቅዱስ መጽሐፍ እንዲህ ሲል ያረጋግጣል። “ከእናንተ መካከል ጥበብ የጎደለው ቢኖር ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን ለእርሱም ይሰጠዋል። ነገር ግን በምንም ሳይጠራጠር በእምነት ይለምን።” (የያዕቆብ መልዕክት ፩፥፭-፯) ስለሆነም በዓሉ የበረከት የሰላምንና ፍቅርን በዓል ይሁንልዎ።
ሊቀ ካህናት ምሳሌ እንግዳ
በካናዳ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ዋና አስተዳዳሪ።
“አሁን ግን ክርስቶስ ላንቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተነስቷል። ሞት በሰው በኩል ስለመጣ ትንሣዔ ሙታን በሰው በኩል ሆኖአልና።” (፩ኛ ቆሮ.፲፭፥፳-፳፩)
የትንሣዔ ፕሮግራም ቅዳሜ ሚያዚያ ፯ ቀን ፪ሺህ፱ ዓ.ም. ከምሽቱ ፲፪ ሰዓት እስከ ሌሊቱ ፯ ሰዓት ተኩል ድረስ ያካሄዳል።
ከምሽቱ ፲፪ ሰዓት የወንጌል ትምህርት።
ከምሽቱ ፪ ሰዓት ፴ የመክፈቻ ጸሎትና ማሕሌት።
ከምሽቱ ፫ ሰዓት ተኩል ጸሎተ ወንጌል ምስባክ።
ዘተንሣዔ
ወተንሥአ እግዚአብሔር ከመ ዘነቃህ እምንዋም ወከመ ኅያል ወኅዳገ ወይን ወቀተለ ፀሮ በድኅሬሁ።
እግዚአብሔርም ከአንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ። የወይን ስካር እንደተወው እንደ ኃያልም ሰው። ጠላቶቹንም በኋላቸው መታ።
መዝሙር ፸፰ ፥ ፷፭ - ፷፮
የማቴዎስ ወንጌል ፳፰ ፥ ፩ - ፲፭
ምልጣን (አንገርጋሪ) እስመ ለዓለም
በዚህ ጊዜ ምዕመናኑ ጧፍ ያበራሉ
የደብሩ ታዳጊ መዘምራን “ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ፤ “ ወረብ ያቀርባሉ።
ከምሽቱ ፬ ሰዓት ከሩብ ኪዳን
ከምሽቱ ፬ ሰዓት ተኩል ቅዳሴ ይጀመራል
የዕለቱ ንባብ፤ ፩ ቆሮንቶስ ፲፭ ፥ ፳ - ፵፩
፩ ጴጥሮስ ፩ ፥ ፩ - ፲፫
የሐዋርያት ሥራ ፪ ፥ ፳፪ - ፴፯
ምስባክ፤ መዝሙር ፸፰ ፥ ፷፭ - ፷፮
ወንጌል፤ የዮሐንስ ወንጌል ፳ ፥ ፩ - ፲፱
ከሌሊቱ ፯ ሰዓት ተኩል ሲሆን ስርወተ ሕዝብ ይሆናል።